ቁርባን (HOLY COMMUNION)

ቁርባን (HOLY COMMUNION)

ምስጢረ ቁርባን፡ የቤተክርስቲያን ምስጢራት አክሊል

ምስጢረ ቁርባን (Mystery of Eucharist) ከአምስቱ አዕማደ ምስጢራት አንዱ ነው፡፡ ሃይማኖታቸው የቀናና እውነተኛ የሃይማኖትን መንገድ ያቀኑ ቀደምት አበው (ሠለስቱ ምዕት) “ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተክርስቲያን እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት (ከሁሉ በላይ በምትሆን የሐዋርያት ጉባዔ በአንዲት ቅድስት ቤተክርስቲያን እናምናለን)” ብለው የሃይማኖትን ድንጋጌ ያስቀመጡት በቅድስት ቤተክርስቲያን ምስጢረ ምስጢራት (የምሥጢራት ሁሉ ማጽኛ ማኅተም) የተባለው ምስጢረ ቁርባን ስለሚፈጸምባት ነው፡፡ ይህም ምስጢር የሌሎች ምስጢራተ ቤተክርስቲያን መክብባቸውና መፈጸሚያቸው ነው፡፡ የሰው ልጆች ድኅነትን (የዘላለም ሕይወትን) የምናገኝበት፣ በክርስቶስ ቤዛነት ያገኘነውን ነፃነት በሥጋዊ ድካም በኃጢአት ስናሳድፈው ደግሞ ለዘለዓለም ሕያው ከሆነ መስዋዕት በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ እየተካፈልን፣ በድቅድቅ ጨለማ የተመሰለ ኃጢአትን ድል አድርገን ለሰርጉ ቤት ለመንግስተ ሰማያት የተገባን የምንሆንበት ምሥጢር ነው፡፡

የምስጢረ ቁርባን ትርጉም ምንድን ነው?

Read More ▼

    ቁርባን ቃሉ የሱርስትና የግሪክ ሲሆን ትርጉሙ በቁሙ መንፈሳዊ አምኃ (ስጦታ)፣ መስዋዕት፣ መባዕ፣ ለአምላክ የሚቀርብ የሚሰጥ ገንዘብ ማለት ነው፡፡ ግብጾች ዩክሪስት ይሉታል፡፡ ይህም ቃል የግሪክ ሲሆን ትርጉሙ ‹‹ምስጋና ማቅረብ›› ማለት ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ‹‹የጌታ እራት››፣ ‹‹ምስጢራዊው እራት››፣ ‹‹አንድ የመሆን ምስጢር›› ይሉታል፡፡ ቁርባን የሚለውን ቃል በስፋት ስንመለከተው ሰው ለአምላኩ (ለፈጣሪው) የሚያቀርበውን አምኃ በሙሉ የሚያካትት ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ የምንመለከተው ግን ስለ አማናዊው ስጦታ ስለኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ነው፡፡ ከሰው ለእግዚአብሔር የቀረበ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ለሰው ሁሉ የተሰጠ የዘላለም ሕይወትን የምንካፈልበት አምላካዊ ጥበብ ነው፡፡ ሰው ለመስዋዕት የሚሆነውን ቀላል ነገር ያቀርባል፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ የሰውን መታዘዝና እምነት አይቶ የሚያልፈውን ወደማያልፈው፣ ምድራዊውን ወደ ሰማያዊው፣ ጊዜያዊውን ወደዘላለማዊው ይለውጣል፡፡ ይህም ምስጢረ ቁርባን በመባል ይታወቃል፡፡
    ከአባታችን አዳም ጀምሮ የነበሩ የብሉይ ኪዳን ቅዱሳን በኃጢአታቸው ከእግዚአብሔር በተለዩ ጊዜ ሁሉ በግና ላምን የመሳሰሉ እንስሳትን በእምነት መስዋዕት አድርገው ያቀርቡ ነበር፤ እግዚአብሔርም መስዋዕታቸውን እየተቀበለ ይታረቃቸው ነበር፡፡ በሕገ ልቡናና በሕገ ኦሪት የነበሩት ሁሉ በዚህ ሥርዓት አልፈዋል፡፡ አበ ብዙሐን አብርሃም ልጁን ይስሐቅን ለመሰዋት ወደ ሞሪያ ተራራ በሚወስደው ሰዓት የክርስቶስ ምሳሌ የሆነ ይስሐቅ አባቱን አብርሃምን የጠየቀው ጥያቄና በመንፈስ ቅዱስ የተቃኘው የአብርሃም ምላሽ በብሉይ ኪዳንና በሐዲስ ኪዳን መስዋዕት መካከል ያለውን መሰረታዊ ልዩነት ያስረዳናል፡፡ በዘመነ ብሉይ መስዋዕቱ ምድራዊ፣ አቅራቢውም ምድራዊ ነው፡፡ ይስሐቅ እንደተለመደው የመስዋዕት በግ እንዳልተያዘ ባየ ጊዜ “አባቴ ሆይ…እሳቱና እንጨቱ ይኸው…የመሥዋዕቱ በግ ግን ወዴት አለ?” በማለት ጠይቆት ነበር፡፡ በአብርሃም ህሊና የመሥዋዕቱ በግ ይስሐቅ ነበር፡፡ ይሁንና መንፈስ ቅዱስ እንዳቀበለው “ልጄ ሆይ የመሥዋዕቱን በግ እግዚአብሔር ያዘጋጃል፡፡” በማለት መለሰለት፡፡ (ዘፍ. 22፡7-8) ለጊዜው እግዚአብሔር ያዘጋጀው (አብርሃምም ይስሐቅም የማያውቁት) ንጹሕ የመሥዋዕት በግ በዕፀ ሳቤቅ ተይዞ ከሰማይ ወረደ፣ በይስሐቅም ቤዛ መሥዋዕት ሆኖ ቀረበ፡፡ (ዘፍ. 22፡13) ይህ በይስሐቅ ፈንታ የተሰዋው ንጹሕ በግ የዓለም መድኃኒት የኢየሱስ ክርስቶስ ምሣሌ ነበር፡፡
    ይስሐቅና አብርሃም ለጊዜው ሳይረዱት በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት ሳይረዱት የመሰከሩለት እውነተኛው፣ እግዚአብሔር ያዘጋጀው (ሰውን ለማዳን በባሕርያችን የተገለጠ) የመሥዋዕት በግ ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን የነቢያት ፍጻሜ፣ የሐዋርያት መጀመሪያ የሆነ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ መስክሮልናል፡፡ “ዮሐንስ ወደ እርሱ ሲመጣ ጌታችን ኢየሱስን አይቶ እንዲህ አለ ‘እነሆ የዓለሙን ኀጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ፡፡ ከእኔ በፊት የነበረ ሰው ከእኔ በኋላ ይመጣል ብዬ ስለ እርሱ የነገርኋችሁ ይህ ነው፤ እርሱ ከእኔ አስቀድሞ ነበርና፡፡” (ዮሐ. 1፡29-30) ስለ ሆነም የሐዲስ ኪዳን እውነተኛ መሥዋዕት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ መሥዋዕትነቱም በይስሐቅ ፈንታ እንደቀረበው በግ ለአንድ ሰው ወይም ለጥቂቶች ሳይሆን ለዓለም ሁሉ ነው፡፡ መሥዋዕት የሆነውም እንደ ብሉይ ኪዳን መሥዋዕት በተደጋጋሚ ሳይሆን አንድ ጊዜ ነው፡፡ መሥዋዕቱም፣ መሥዋዕት አቅራቢውም፣ መሥዋዕት ተቀባዩም እርሱ ራሱ ሰው የሆነ አምላክ፣ ልዩ ሊቀ ካሕናት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ምሥጢረ ቁርባን ማለት ከዚህ በታች በተብራራው መሰረት አንድ ጊዜ ስለ ዓለም ሁሉ ቤዛ መሥዋዕት ከሆነ ከኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም አካሉ እንሆን ዘንድ የምንካፈልበት፣ ከክርስቶስ ለቤተክርስቲያን የተሰጠ የጸጋዎች ሁሉ አክሊል ነው፡፡ ደጉ አባታችን አባ ሕርያቆስ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት በተናገረው የቅዳሴ ማርያም አንቀጽ ይህንን ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፡- “ዛሬ በዚህች ቀን በፍቅርና በትሕትና ግሩም በሚሆን በዚህ ምሥጢር ፊት እቆማለሁ፡፡ በዚህም ማዕድና ቁርባን ፊት፡፡ መንፈሳቸውን ያረከሱ ሰዎች ከርሱ ሊቀምሱ የማይቻላቸው በእውነት ቁርባን ነው፡፡ በበግ በጊደርና በላም ደም እንደ ነበረው እንደ ቀደሙት አባቶች መሥዋዕት አይደለም፤ እሳት ነው እንጂ፡፡ ፈቃዱን ለሚሠሩ ልቡናቸውን ላቀኑ ሰዎች የሚያድን እሳት ነው፡፡ ስሙን ለሚክዱ ለዓመፀኞች ሰዎች የሚበላ እሳት ነው፡፡” (ቅዳሴ ማርያም ቁጥር 5-7)
    በእግዚአብሔር አንድነትና ሦስትነት (በምስጢረ ስላሴ) አምነው በክርስቶስ ደም የተዋጁና በአብ፣ በወልድ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተጠመቁ ምዕመናን የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም በመቀበል ምስጢረ ቁርባንን ይፈጽማሉ፡፡ ጌታም በቃሉ ‹‹ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው›› (ዮሐ 6፡54) ብሎ እንደተናገ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን የሚቀበሉ ምዕመናን የዘላለም ሕይወት አላቸው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ሳይገባው ይህንን እንጀራ የበላ ወይም የጌታን ጽዋ የጠጣ ሁሉ የጌታ ሥጋና ደም ዕዳ አለበት›› (1ኛ ቆር 11፡26) ብሎ እንደገለጸው የምስጢረ ቁርባን ተካፋይ የሆነ ሁሉ ስለ ቅዱስ ቁርባን ትርጉም፣ አስፈላጊነት፣ አፈጻጸም …ወዘተ ማመንና ማወቅ ይጠበቅበታል፡፡

    የሐዲስ ኪዳን ቁርባን በማን እና እንዴት ተመሠረተ?

    ምስጢረ ቁርባንን የመሠረተው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ ‹‹ሲበሉም ኢየሱስ እንጀራውን አንስቶ ባረከ፤ ቆርሶም ለደቀመዛሙርቱ ሰጠና እንካችሁ ብሎ ይህ ሥጋዬ ነው አለ፡፡ ጽዋውንም አንስቶ አመስግኖ ሰጣቸው፡፡ ሁላችሁም ከእርሱ ጠጡ፤ ስለብዙዎች የኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የሐዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው፡፡›› (ማቴ 26፡26) በማለት የምስጢረ ቁርባንን አመሠራረት ጽፎታል፡፡ አስቀድሞ በብሉይ ኪዳን ሲቀርቡ የነበሩ መስዋዕቶችን ሁሉ ምሳሌው አድርጎ በማሳለፍ የራሱን መስዋዕትነት ካቀረበ በኋላ ቀድሞ የነበሩትን ነፍሳት ብቻ ሳይሆን ከዚያም በኋላ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድርስ የሚመጡትን ሁሉ አንድ ጊዜ ባቀረበው መስዋዕት የሚያድን ስለሆነ ምስጢሩ ይፈጸም ዘንድ ከሞቱ አስቀድሞ አስተማረ፡፡ ‹‹እውነት እውነት እላችኋለሁ የወልደ እጓላ እመሕያው ክርስቶስን ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም፡፡ ‹‹ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው›› በማለት እስከዓለም ፍጻሜ የሰው ልጅ ሌላ መስዋዕት ሳያስፈልገው በአምላካችን ሥጋና ደም ሕይወት እንደሚያገኝ አስተማረ፡፡ የምስጢረ ቁርባንን ትምህርት በወቅቱ የነበሩ አይሁድ ሰምተው ምስጢሩ አልገባቸው ሲል ‹‹ይህ ሰው ሥጋውን ልንበላ ይሰጠን ዘንድ እንዴት ይቻላል›› በማለት ጠይቀው ነበር፡፡ ደቀመዛሙርቱም ትምህርቱ ከብዷቸው ነበር፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደ በኋላ ግን ምስጢሩን ተረድተው ሲፈጽሙ ቆይተዋል፡፡ (ሐዋ 2፡43፣ 1ኛ ቆሮ 11፡20)

    ከምስጢረ ቁርባን በመሳተፍ የሚገኘው ጸጋ ምንድን ነው?

    የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ስንቀበል የምናገኘው በረከትና ጸጋ ስፍር ቁጥር ባይኖረውም እንኳን የሚከተሉትን በዓበይትነት ማግኘት እንችላለን፡፡
    1. ቅዱስ ቁርባን የዘላለም ሕይወት ያሰጠናል፡፡ ጌታችን በማይታበል አማናዊ ቃሉ ‹‹ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሳዋለሁ›› በማለት እንደተናገረ የተቀበልነው ቅዱስ ቁርባን የሕያው አምላክ የኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም ነውና የዘላለም ሕይወት ባለቤት መሆናችንን ያረጋግጣል፡፡ ዳግመኛም ቅርጫፍ ከግንዱ እስካልተለየ ድረስ ልምላሜ፣ ጽጌና ፍሬ ሕይወት ለዘላለም እንዲኖረው ሁሉ ክርስቲያኖችም ጉንደ ሐረገ ወይን ከሆነው ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ አለመለየታችንና በሕይወት መኖራችንን ቅዱስ ቁርባን ስንቀበል እናረጋግጣለን፡፡ (ዮሐ 6፡53፣ ሮሜ 11፡21-24) ሕያዋን የሚያደርጉንም በውስጣችን ያደረው (የተዋሐደን) ሥጋ ክርስቶስና ደመ ክርስቶስ ናቸው፡፡ እርሱ የማይሞት የማይለወጥ ነውና ‹‹ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል፤ እኔም በእርሱ እኖራለሁ›› በማለት አረጋግጦልናል፡፡ (ዮሐ 6፡56)
    2. ቅዱስ ቁርባን ሥርየተ ኃጢአትን ያስገኛል፡፡ አባቶቻችን ‹‹ሰው ሆኖ የማይበድል እንጨት ሆኖ የማይነድ የለም፤ ከሰው ስህተት ከብረት ዝገት አይጠፋም›› እንዲሉ ደካማና ስሑት የሚሆን ሰብአዊ ባሕርያችን ወደ ስህተት ጎዳና ሲነዳንና ኃጢአት ሲያገኘን በደላችንን ለካህን ተናዝዘን፣ ቀኖና ተቀብለንና ንስሐችንን ጨርሰን በካህኑ ፈቃጅነት ቅዱስ ቁርባንን ስንቀበል የቀደመ ኃጢአት በደላችን ሁሉ እሳት ላይ እንደወደቀ ቅቤ ቀልጦ ጠፍቶ ነጻ ያደርገናል፡፡ ‹‹ከጥምቀት በፊት የተሠራ ኃጢአት በጥምቀት ይሰረያል፤ ከጥምቀት በኋላ የተሠራ ኃጢአት በንስሐና በሥጋ ወደሙ ይሰረያል›› እንዳለ ፊልክስዮስ፡፡ የጌታ ሥጋና ደም ሥርየተ ኃጢአትን ያሰጣልና፡፡ ‹‹ ስለብዙዎች የኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የሐዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው፡፡›› (ማቴ. 26፡28) ብሎ ባለቤቱ ራሱ አስረድቶናል፡፡ እንግዲህ እናስተውል ሥጋውን ከመቁረሱ ደሙን ከማፍሰሱ በፊት በአንጻረ ሕብስትና ጽዋ ሥጋውንና ደሙን ባርኮ ሰጥቶናል፡፡ ይህም እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ የክርስቶስ አካል የሆነች ቅድስት ቤተክርስቲያን ኃጢአትን የሚያስተሰርይ የጌታን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ለምዕመናን የምትሰጥበት ሰማያዊ ሥርዓት ነው፡፡ የከበረ ሐዋርያ ቅዱስ ዮሐንስ “ልጆቼ ሆይ እንዳትበድሉ ይህን እጽፍላችኋለሁ፤ የሚበድልም ቢኖር ከአብ ዘንድ ጰራቅሊጦስ አለን፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ኃጢአታችንን ያስተሰርይልን ዘንድ ጻድቅ ነው፡፡” (1ኛ ዮሐ. 2፡1) በማለት እንደመከረን በደካማ ባሕርይ እግዚአብሔርን የሚያሳዝን በደል ብንፈጽም በንስሐ ተመልሰን የእግዚአብሔርን ማዳን የምናገኝበት ህያው ቃል ኪዳን የእግዚአብሔር የቸርነቱ መገለጫ የሆነ ቅዱስ ቁርባን ነው፡፡ ማንኛውም ሰው በሃይማኖት ሆኖ ቅዱስ ቁርባንን ቢቀበል ሥርየተ ኃጢአትን ያገኛል፡፡ ከኃጢአት ቁራኝነት ነጻ ሆኖ ኅብረቱ ከሰማያውያን ቅዱሳን ጋር ይሆናል፡፡ ‹‹ኅብስቱ አንድ እንደሆነ እንዲሁም እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ አካል ነን፡፡ ሁላችንም ከአንድ ኅብስት እንቀበላለንና›› በማለት ንዋየ ኅሩይ ቅዱስ ጳውሎስ ያረጋግጥልናል፡፡ (1ኛ ቆሮ 10፡17)
    3. ቅዱስ ቁርባን የኃጢአት ልጓም ሆኖ ያገለግለናል፡፡ ክርስቲያን የጌታን ሥጋና ደም ሲቀበል የኃጢአት ልጓም ያገኛል፡፡ ሥጋው ለኃጢአት የሚጓጓና የሚሰነካከል እንዳይሆን የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይጠብቀዋል፡፡ በሥጋውና በደሙ የተዋሐደው አምላክ ኃጢአትን ተደፋፍሮ እንዳይሠራ ይወቅሰዋል፡፡ የኃጢአት ውጤት ሞት መሆኑን ያሳስበዋል፡፡ በአጠቃላይ ወደ ቅድስናና ጽድቅ የሚመራ መንፈሰ እግዚአብሔር ስለተዋሐደን ለጽድቅ ሥራ የምንተጋ ለኃጢአት የምንሰቀቅ እንሆናለን፡፡ በቅዱስ ቁርባን ጸጋ እግዚአብሔርን ስለምንታደል ኃጢአትን እንጸየፈዋለን፡፡ ምክንያቱም በመንፈሳዊ ዕውቀት የምናድግበትና በጸጋ መንፈስ ቅዱስ የምንበለጽግበት ምግበ ሕይወት አግኝተናልና ነው፡፡ ‹‹የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፡፡ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም፡፡ በእኔ የሚያምን ሁል ጊዜ ከቶ አይጠማም….ሥጋዬ እውነተኛ መብል ደሜ እውነተኛ መጠጥ ነውና›› (ዮሐ 6፡35-45) እንዲል፡፡

    . ምስጢረ ቁርባን ስለምን የምስጢራት ሁሉ መክብባቸው/አክሊል

    ቅዱስ ቁርባን ለሰባቱ ምስጢራተ ቤተክርስቲያን አክሊል ነው፡፡ እንዲያውም ምስጢረ ምስጢራት ይባላል፡፡ ምክንያቱም አንድ ተጠማቂ ተጠምቆ እንደወጣ ቅዱስ ቁርባን መቀበል አለበት፡፡ አንድ ተነሳሒ ቀኖናውን ሲጨርስ በካህኑ ፈቃድ ንስሐውን በቅዱስ ቁርባን ያትመዋል፡፡ በቅዱስ ጋብቻ ለመኖር የወሰኑ ተጋቢዎች ከሥርዓተ ተክሊል በኋላ አስቀድሰው ቅዱስ ቁርባንን ይቀበላሉ፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች ቅዱስ ቁርባን የምስጢራት ምስጢር መባሉ ትክክል ነው፡፡ ቅዱስ ቁርባን የምስጢራተ ቤተክርስቲያን ሁሉ የበላያቸው፣ መክብባቸውና መፈጸሚያቸው የሆነበት ምክንያት ጌታ የሰውን ልጅ ለማዳን በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ ሥጋውን በመቁረስ ደሙንም በማፍሰስ ካሳ የከፈለበትን፣ የማዳን ሥራውን የፈጸመበትን ሁኔታ የሚያረጋግጥና የሚመሰክር ከመሆኑ ጋር ምዕመናን ከሥጋውና ከደሙ ተካፋይ እንዲሆኑ በማብቃት የሕይወትን ጸጋ እንዲቀበሉ ስለሚያደርግ ነው፡፡ ስለዚህም ሌሎቹ ምስጢራት ሁሉ በቅዱስ ቁርባን አማካኝነት የምስጢራቸውን ትርጉምና ፍጻሜ ያገኛሉ፡፡

    ክርስቶስ ሥጋውንና ደሙን ለምን በምግብና መጠጥ (በሚበላና በሚጠጣ) አደረገው?

    ምግብና መጠጥ ከሰውነታችን እንደሚዋሐድ ሥጋውንና ደሙን ስንቀበል በእውነት እንደሚዋሐደን ለማስረዳት፤ በጸጋ ተዋሕጃችኋሁ ሲለን ሥጋውና ደሙን በሚበላና በሚጠጣ አደረገው፡፡ አንድም መብልና መጠጥ ያፋቅራል፤ ስጋና ደሙ ያፋቅራልና፤ ቅዱስ ቁርባንም የክርስቶስን ፍቅር በልቦና ያሳድራልና አንድም እርሱ ለእኛ ያለውን ፍቅር ሲገልጥልን ሥጋውና ደሙን በሚበላና በሚጠጣ አደረገው፡፡ እንዲሁም ምግብ ለሥጋችን ኃይል እንደሚሆነን ሥጋውና ደሙም ለነፍሳችን መንፈሳዊ ኃይል እንዲሰጠን ሥጋውና ደሙን በሚበላና በሚጠጣ አደረገው፡፡ በተጨማሪም በመብል የጠፋው ዓለም በመብል እንዲድን፤ አዳምና ሄዋን በምግብ የእግዚአብሔር ልጅነታቸውን እንዳስወሰዱ ፤ በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ ልጅነታችንን ሊመልስልን ሥጋውና ደሙን በሚበላና በሚጠጣ አደረገው። (ዘፍ 3 ፥ 1 ። ዮሐ 6 ፥ 49) ከዚህም በላይ የተራበና የተጠማ ሰው ብር፣ ወርቅ ከሚሰጡት ይልቅ መብልና መጠጥ የሰጠውን እንደሚወድ ጌታም ፍቅሩን ሲገልጥልን የነፍስ ርሃባችንን ሊያስወግድ ሥጋና ደሙን በምግብና በመጠጥ አደረገው፡፡ ምግብና መጠጥ በቀላሉ ከሰውነታችን እንደሚዋሐድ እንዲሁ ጌታም በቀናች ሃይማኖት በመልካም ምግባር ሆነን ሥጋውን ብንበላ ደሙንም ብንጠጣ ከጌታችን ሕያውነት የተነሳ ለዘለዓለም ሕያው ሆነን በክብር እንደምንኖር ጌታችን አስተምሮናል፡፡ (ዮሐ. 6፡58)

    የቅዱስ ቁርባን የብሉይ ኪዳን ምሳሌዎች ምንድን ናቸው?

    1. የአብርሃም መሥዋዕት፡ አባታችን አብርሃም በልጁ ይስሐቅ ፈንታ የሰዋው በግ ለአማናዊው (ለእውነተኛው) የእግዚአብሔር በግ ለጌታችን ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀጥተኛ ምሳሌ ነው፡፡ አብርሃም በጉን በይስሐቅ ፈንታ እንደሰዋ ሁሉ ክርስቶስም ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ መስዋዕት (ምትክ) ሆኖ ተሰውቷል፡፡ የበጉ ቀንድ በዕፀ ሳቤቅ ተይዞ እንደተገኘ ጌታም ከእመቤታችን በነሳው ሥጋ ተገኝቷል፡፡ አብርሃም በሰዋው በግ እርሱና ዘሮቹ በሙሉ እንደተባረኩ፣ በጌታም መስዋዕትነት አዳምና ልጆቹ ተባርከዋል፡፡ ዘፍ 22፡1-9
    2. መሥዋዕተ መልከጼዴቅ፡ መልከ ጼዴቅ ከአብርሃም በፊት የነበረ የእግዚአብሔር ካህን ነው፡፡ዘፍ 14፡18-21 ዕብ 7፡1 ከመልከጼዴቅ በኋላ የተነሡ ሌዋውያን ካህናት መሥዋዕትን የሚያዘጋጁት ከእንስሳት ነበር፡፡ ዕብ 10፡4 መልከጼዴቅ ግን የሐዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን ራስ የክርስቶስ ምሣሌ ነበርና እንደ ሐዲስ ኪዳን ሥርዓት በንጹህ ስንዴና ወይን ያስታኩት ነበር፡፡ ይህንንም መሥዋዕት አድርጎ ያቀርብ ነበር፡፡ ‹‹የእንስሳትን መስዋዕት አትሰዋ፤ ነገር ግን መስዋዕትህ በእግዚአብሔር ፊት ከንጹሕ የስንዴ ኅብስትና ከንጹሕ የወይን ፍሬ ይሁን›› እንዳለ ቀለሜንጦስ፡፡ መሥዋዕተ መልከጼዴቅ ለቅዱስ ቁርባን ምሳሌው ነበር፡፡ የመልከ ጼዴቅ ክህነትም ለኢየሱስ ክርስቶስ ዘላለማዊ ክህነት ምሳሌ ነበር፡፡
    3. የደብተራ ኦሪት ቁርባንና መሥዋዕት፡ ከ430 ዓመታት በኋላ ከግብፅ የወጡት እስራኤላውያን መሥዋዕትን እንዲያቀርቡ ታዘው ነበር፡፡ ዘሌ 12፡3-11 ይህ የበግ መሥዋዕት የሚቀርብበት የእስራኤል ፋሲካ የሥጋ ወደሙ ምሳሌ ነበር፡፡በዕብራይስጥ ፋሲካ ማለት ‹‹አለፈ›› ማለት ነው፡፡ያለፈውም ቀሳፊው መልአክ ነው፡፡ በሐዲስ ኪዳን ክርስቶስ ‹‹ፋሲካችን›› ተብሏል፡፡ 1ኛ ቆሮ 5፡7 ‹‹በዓለ ትንሣኤ ፋሲካነ እስመ ሥርዓቱ ለእስራኤል ውእቱ›› እንዲል፡፡
    4. እስራኤል ከሞተ በኩር የዳኑበት በግ፡ ሕዝበ እስራኤል በእግዚአብሔር ኃይል በሙሴ መሪነት ከፈርዖን መዳፍ ነጻ የወጡት በግብፃውያን ላይ በታዘዘው ሞተ በኩር ምክንያት ነበር፡፡ ይህ ሞተ በኩር የእስራኤልን ልጆች እንዳያገኛቸው ‹‹ነውር የሌለበት የአንድ ዓመት ጠቦት እንዲያዘጋጁ፣ እስከ 14ኛው ቀንም እንዲጠብቁት፣ሲመሽም እንዲያርዱት፣ ከደሙም ወስደው በሚበሉበት ቤት ሁለቱን መቃንና ጉበኑን እንዲቀቡት፣ በእሳት የተሠበሰውን ሥጋውንና ቂጣውን እንጀራ እንዲበሉ፣ የቀረውንም እንዲያቃጥሉት›› ታዘው ነበር፡፡ ነውር የሌለበት የአንድ ዓመት ጠቦት ምክንያተ ኃጢአት የሌለበት የንጹሐ ባሕርይ አምላክ የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ የበጉን ጥብሱን ብቻ እንደተመገቡ በእሳት የተመሰለ መለኮት የተዋሐደውን ሥጋ ለምንቀበል ለእኛ አብነት ለመሆን የምንበላውና የምንጠጣው ሥጋና ደም ነፍስ የተለየው መለኮት የተዋሐደው ነውና፡፡ ዘጸ 12፡46
    5. ለእስራኤል የወረደው መና፡ ለእስራኤል ልጆች በምድረ በዳ ከደመና የወረደላቸው መና ጌታ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ ለሰው ልጆች ሲል የቆረሰው ሥጋና ያፈሰሰው ደም ምሳሌ ነው፡፡ መናው የተገኘው ከደመና እንደሆነ ሁሉ ጌታም ሥጋና ነፍስን የነሳው ከቅድስት ድንግል ማርያም ነው፡፡ ስለዚህ ደመናው ጌታ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍስዋ ነፍስ ነስቶ ሰው የሆነባት የድንግል ማርያም ምሳሌ ነው፡፡ ጌታም በዘመነ ስብከቱ ‹‹የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፡፡ አባቶቻችሁ በምድረ በዳ መና በሉ ሞቱም፤ ሰው ከእርሱ በልቶ እንዳይሞት ከሰማይ አሁን የወረደ እንጀራ ይህ ነው….እኔም ስለ ዓለም ሕይወት የምስጠው እንጀራ ሥጋዬ ነው›› በማለት ለእስራኤል የወረደው መና የሥጋውና የደሙ ምሳሌ መሆኑን አስተምሯል፡፡ ዮሐ 6፡49-51

    ቅዱስ ቁርባን ለምን ከስንዴና ከወይን ይዘጋጃል?

    ከአዝዕርት ስንዴ ከፍራፍሬ ደግሞ ወይን ለጌታ ሥጋና ደም መመረጣቸው ምሳሌ፣ ትንቢትና ምስጢር አለው፡፡ ምሳሌው ክህነቱ ለወልደ እግዚአብሔር ለኢየሱስ ክርስቶስ ክህነት ምሳሌ ሆኖ የተጠቀሰው መልከጼዴቅ በስንዴና በወይን ይሰዋ ነበር፡፡ ይህም ምሳሌነቱ ለጌታ ሥጋና ደም ነው፡፡ ዘፍ 14፡18 ትንቢቱ ደግሞ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ‹‹በልቤ ደስታ ጨመርኩ፤ ከስንዴ ፍሬና ከወይን ከዘይትም ይልቅ በዛ›› በማለት የተናገረው ነው፡፡ መዝ 4፡7 ምስጢሩ ደግሞ ስንዴ ስብን ይመስላል፤ ወይን ደግሞ ትኩስ ደምን ይመስላል፡፡ ስለዚህ በሚመስል ነገር መስጠቱ ነው፡፡

    መሥዋዕቱ ከቤተልሔም ተነስቶ ወደ ቤተመቅደስ መግባቱ የምን ምሳሌ ነው?

    መሥዋዕቱ የሚዘጋጀው በቤተክርስቲያን ቅጥር (አጥር) ውስጥ በስተምሥራቅ በኩል በሚገኘው ‹‹ቤተልሔም›› ውስጥ ነው፡፡ ይህም ጌታችን በተወለደበት ከተማ ስም የተሰየመ ሲሆን ቤተመቅደሱ ደግሞ አምሳለ ቀራኒዮ ነው፡፡ ጌታችን የማዳን ሥራውን በቤተልሔም ጀምሮ በቀራኒዮ አደባባይ በመልዕልተ መስቀል ላይ ተሰቅሎ ‹‹ተፈፀመ›› በማለት አድኖናልና የቅዱስ ቁርባን መስዋዕትም በቤተልሔም ተዘጋጅቶ ወደ ቤተመቅደስ ገብቶ ይቀርባል፡፡ ይህም ጌታን ከልደቱ እስከ ስቅለቱ ያደረገው የማዳን ጉዞ ምሳሌ ነው፡፡

    ኅብስቱና ወይኑ ወደ ክርስቶስ ሥጋና ደም የሚለወጥበት ሥርዓት ምንድን ነው?

    ምስጢረ ቁርባን የሚከናወንበት ጸሎተ ቅዳሴ እጅግ የከበረና ለክርስቲያኖች ሁሉ በረከትን የሚያሰጥ ነው፡፡ በጸሎተ ቅዳሴው ውስጥ ካህኑ እንደ ሥርዓቱ እየጸለየ በኅብስትና በወይኑ ላይ ቡራኬ ያደርጋል፡፡ ጸሎተ ቅዳሴውንም ሲጸልይ “አቤቱ ወደዚህ ኅብስትና ወደዚህ ወይን መንፈስ ቅዱስንና ኃይልን እንድትልክ እንለምንኃለን፣ የጌታችንን የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውንና ደሙን ያደርገው ዘንድ” የሚለዉን ጸሎት እየጸለየ ቀዳሹ ካህን ሕብስቱንና ወይኑን ይባርካል፡፡ ይህን የሚጸለይበት ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል (በመንፈስ ቅዱስ ሥራ)ኅብስቱ የክርስቶስ ሥጋ፣ ወይኑ የክርስቶስ ደም ይሆናል፡፡ ይህም ጸሎት ይረስዮ ይባላል፡፡ (ኅብስቱንና ወይኑን የክርስቶስ ሥጋውንና ደሙን ያድርገው ማለት ነው)፡፡
    ይህም በቅዳሴ ሐዋርያትና በቅዳሴ እግዚእ ነው ያለው፣ በሌሎቹ ቅዳሴዎችም ይህን የመሰለ ጸሎት አለ፣ ከዚህ ቀጥሎ አያይዞ ካህኑ እየመራ፣ ሕዝቡ እየተከተለ “ሀበነ ንኀበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ ወፈውሰነ በዝንቱ ጵርስፎራ…” እያሉ ይጸልዩበታል፡፡ ቀጥሎ ጸሎተ ፈትቶ አለ፣ ቄሱ ያን እየጸለየ እንደ ሥርዓቱ ሥጋውን ይፈትተዋል፡፡ ይህንንም ሲፈጽም ካህኑ እየመራ ሕዝቡ እየተቀበሉ አርባ አንድ ጊዜ እግዚኦታ (እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ) ያደርሱበታል፡፡ ቀጥሎ ካህኑ “አአምን፣ አአምን፣ አአምን፣ ወእትአመን …እያለ ሥጋውን በደሙ” “ቡሩክ እግዚአብሔር አብ…ወብሩክ ወልድ ዋሕድ…ወቡሩክ መንፈስ ቅዱስ…”እያለ ደሙን በሥጋው ሦስት፣ ሦስት፣ ጊዜ ይባርከዋል፡፡ ከዚህ በኋላ በቅድሚያ ቀዳሾች ካህናት (ቅዱስ ሥጋውን ከሠራዒው ካህን፣ ክቡር ደሙን ከንፍቁ ካህን እጅ በዕርፈ መስቀል)፣ ቀጥሎ ሕዝቡ (ቅዱስ ሥጋውን ከሠራዒው ካህን፣ ክቡር ደሙን ከዲያቆኑ በዕርፈ መስቀል) እንቀበላለን፡፡

    ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን ሊቀበል የሚገባው ማነው? ሕጻናትና ለአዛውንቶች ብቻ ናቸውን? <

    ለብዙዎች የክርስቶስ ሥጋና ደም ለሕፃናት፣ ለአረጋውያንና በደዊ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ ለተያዙ ብቻ የተሰጠ ይመስላቸዋል፡፡ ይህ ግን ፍጹም ስሕተት ነው፡፡ ሥጋ ወደሙ የዘላለም ሕይወትን የሚያድል፣ ሥርየተ ኃጢአትን የሚሰጥና ከዳግም ድቀት የሚጠብቅ ነው ካልን ይህ ጸጋና በረከት ደግሞ ዕድሜ፣ዘር፣ ቀለምና ጾታ ሳይለይ በስሙ ለሚያምኑ የሰው ልጆች ሁሉ የሚያስፈልግ መሆኑ ጥርጥር የለውም፡፡ ጌታችን ኅብስቱን ከ13 ፈትቶ አንዱን ራሱ ተቀብሎ የቀረውን ያቀበላቸው 13ቱን ሕማማተ መስቀል ተቀብዬ አድናችኋለሁ ሲላቸው ነው፡፡ ሥጋዬን በልታችሁ ደሜን ጠጥታችሁ መንግስተ ሰማያት ትገባላችሁ ቢላቸው ከአይሁድ ትምህርት የተነሳ የሰው ሥጋ እንዴት ይበላል ብለው ይፈሩ ነበርና አብነት ሲሆናቸው ቆርቦ አቆረባቸው፡፡
    በማዕከለ ምድር በቀራኒዮ አደባባይ በመልዕልተ መስቀል ላይ የተሰዋው የመድኃኒት በግ ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ትምህርቱ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ለሚያምንበት ሁሉ የተሰጠ ምግበ ሕይወት መሆኑን አስተምሯል፡፡ የአዳም ዘር የሆነ ሁሉ መንግስተ እግዚአብሔርን ይወርስ ዘንድ ከዚህ መንፈሳዊ አምኃ (ስጦታ) መካፈል ግዴታው ነው፡፡ ሰው አስቀድሞ የሚቀበለው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ አማናዊ መሆኑን አምኖ ራሱን ሲመረምር፣ ንስሐ ሲገባና ከመምህረ ንስሐው ጋር ተማክሮ በሃይማኖትና በአትሕቶ ርዕስ ቢቀርብ ከቅዱስ ቁርባኑ አይከለከልም፡፡ 1ኛ ቆሮ 11፡29 ስለዚህ በክርስቶስ የባህርይ አምላክነት ያመነ፣ ሃይማኖታዊ ምስጢር የገባው፣ ንስሐ የገባና የተሰጠውንም ቀኖና በሚገባ የፈጸመ ሰው ዕድሜና ጾታ ሳይለይ ከምስጢረ ቁርባን መካፈል ይችላል፡፡

    ከምስጢረ ቁርባን ለመሳተፍ ምን ዝግጅት ያስፈልጋል?

    እንኳንስ ሥጋ ወደሙን የሚቀበል ክርስቲያን ይቅርና ወደ አንድ ምድራዊ ንጉሥ (ባለ ጸጋ) ግብዣ የተጠራ ሰው አቅሙ የፈቀደለትን ያህል ተዘጋጅቶ ነው የሚሄደው፡፡ ለሰማያዊው ንጉሥ ለኢየሱስ ክርስቶስ ግብዣማ አብልጠን ልንዘጋጅ ይገባል፡፡ ማቴ 21፡16 ‹‹ንጉሥ የተቀመጡትን ለማየት በገባ ጊዜ በዚያ የሰርግ ልብስ ያልለበሰ ሰው አየና ወዳጄ ሆይ የሰርግ ልብስ ሳትለብስ እንዴት ወደዚህ ገባህ አለው፤ እርሱም ዝም አለ›› ይለናልና እኛም ጥያቄው ምላሽ እንዳናጣ ልንዘጋጅ ያስፈልጋል፡፡
    ስንዘጋጅም ወደ ልባችን የኃጢአት ሐሳብ እንዳያስገቡ አካለዊ ስሜቶቻችንን ሁሉ መግዛት፣ አካልን መታጠብና አቅም የፈቀደውን ንጹሕና ጽዱ (ነጭ) ልብስ መልበስ (ራዕ 6፡11)፣ ቁርባን በሚቀበሉበት ዋዜማ ቀለል ያለ ምግብ መመገብና ለ18 ሰዓታት ከምግበ ሥጋ መከልከል፣ በትዳር ለሚኖሩ ከቁርባን በፊት ለ3 ቀናት ከቁርባን በኋላ ለ2 ቀናት ከሩካቤ መከልከል፣ ለወንዶች ህልመ ሌሊት (ዝንየት) ለሴቶች ደግሞ የወር አበባ (ወይም በማንኛውም ምክንያት የሚደማ/የሚፈስ፣ ቁስል) ያላገኛቸው፣ ሴቶች ወንድ ቢወልዱ 40 ቀን ሴት ቢወልዱ ደግሞ 80ቀን የሞላቸው፣ በሚቆርቡበት ዕለት ቅዳሴ ሲጀመር ጀምሮ ተገኝቶ ማስቀድስ ናቸው፡፡

    “ከበደላችሁ ንጹሕ ነኝ!” የሚለው የካህኑ አዋጅ ለምን አስፈለገ?

    በቅዳሴ ውስጥ ካህኑ “ንጹሕ የሆነ ከቁርባኑ ይቀበል፤ ንጹሕ ያልሆነ ግን አይቀበል፤ ለሰይጣንና ለመልእክተኞቹ በተዘጋጀው በመለኮት እሳት እንዳይቃጠል፤ በልቡናው ቂምን የያዘ ልዩ አሳብም ያለበት ቢኖር አይቅረብ፤ እጄን ከአፍአዊ ደም ንጹሕ እንዳደረግሁ እንዲሁም ከሁላችሁ ደም ንጹሕ ነኝ፡፡ ደፍራችሁ ወደ ክርስቶስ ሥጋና ደም ብትቀርቡ ከእርሱ ለመቀበላችሁ መተላለፍ የለብኝም በደላችሁ በራሳችሁ ይመለሳል እንጅ፡፡ በንጽሕና ሆናችሁ ባትቀርቡ እኔ ከበደላችሁ ንጹሕ ነኝ” ብሎ እጁን ይታጠባል፡፡ ዲያቆኑም ተቀብሎ “ይህን የቄሱን ቃል ያቃለለ ወይም የሳቀና የተነጋገረ ወይም በቤተክርስቲያን በክፋት የቆመ ቢኖር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዳሳዘነው በእርሱም እንደተነሣሣ ይወቅ ይረዳ ስለበረከት ፈንታ መርገምን ስለኃጢአት ሥርየት ፈንታ ገሃነመ እሳትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ይቀበላል” ይላል፡፡
    ይህ አዋጅ የሚታወጀው ከቅዱስ ሥጋና ከክቡር ደሙ ርቀን እንድንቆም ወይም ተመልካቾች ብቻ እንድንሆን ተፈልጎ ወይም እንዳንቆርብ ለማስፈራራት ተብሎ አይደለም፡፡ ንስሓ ገብተን፣ በምክረ ካህን ተዘጋጅተን በንጽሕና ሆነን እንድንቀበል ነው ለማሳሰብ ነው እንጅ፡፡ የጌታችን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ከኃጢአት በንስሐ ሳይነጹ በድፍረት ቢቀበሉት ቅጣትን ያመጣልና፡፡ ጠላት ዲያብሎስ ግን ይህንን የካህኑን አዋጅ እያሳሰበና እንደማስፈራሪያ እንድናየው እያደረገ “ሥጋ ወደሙን ለመቀበል የበቃህ/ሽ አይደለህ/ሽም” ብሎ ከሥጋ ወደሙ እንድንርቅ ያደርገናል፡፡ የዚህ አዋጅ ዋና መልእክት ንስሓ ገብታችሁ፣ ከንስሓ አባታችሁ ጋር ተማክራችሁ ቅረቡ የሚል ነው፡፡
    ምስጢረ ቁርባን በክርስቶስ ቤዛነት ያመንን ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ የምንሆንበት፣ ስርየተ ኃጢአትን የምናገኝበት፣ በመዳን ጉዞ ውስጥ ሰይጣንን ድል የምናደርግበት፣ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር መሆኑ የሚታወቅበት፣ በእምነት ካልሆነ በቀር በፍጥረታዊ አዕምሮ የማይታወቅ ሰማያዊ ጸጋን የሚሰጥ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፡፡ የበጎ ነገር ጠላት ዲያብሎስ ምዕመናን በቀናች ሃይማኖት ጸንተው ከዚህ ጸጋ እንዳይካፈሉ በመናፍቃን እያደረ የማሳሳቻ ትምህርቶችን ያመጣል፡፡ ስለሆነም ምስጢረ ቁርባን እጅግ ብዙ ጥያቄዎች የሚነሱበት የቤተክርስቲያን ምስጢር ነው፡፡ ሰዎች በዚህ ምስጢር ላይ ጥያቄዎችን የሚያነሱት ስለ ምስጢሩ ካላቸው ግነዛቤ ማነስና ምስጢሩም ከሰው አዕምሮ በላይ ከመሆኑ የተነሳ ነው፡፡ በተጨማሪም ዘመኑ የወለዳቸው መናፍቃንም ራሳቸው ክደው ሌላውንም ለማስካድ በተለያየ መንገድ የሚረጩት የሐሰት ትምህርት በምዕመናን አዕምሮ ውስጥ ብዙ ጥያቄዎች እንዲፈጠሩ ያደርጋል፡፡ ይህንን ከግንዛቤ በማስገባት በአስተምህሮ የጡመራ መድረክ በዚህ ርዕስ ክፍል አንድ ጦማር በምስጢረ ቁርባን ዙሪያ የሚነሱ 12 ዋና ዋና ጥያቄዎች ተዳስሰዋል፡፡ በዚህ በሁለተኛውና የመጨረሻው ክፍል ደግሞ ሌሎች በምስጢረ ቁርባን ላይ የሚነሱ 13 ተጨማሪ ጥያቄዎች ይዳሰሳሉ፡፡

    ቅዱስ ቁርባንን በምንቀበልበት ጊዜ ምን ማድረግ ይጠበቅብናል?

    ጌታችን በቃሉ እንዳስተማረን ቅዱስ ቁርባን ደካማ ስጋችን በእግዚአብሔር ፀጋ ከብሮ የሚኖርበት ድንቅ ምሥጢር ነው፡፡ በኃጢአት የደከመ ሰውነታችን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ለመሆን፣ የክርስቶስን ሥጋና ደም ለመቀበል በንስሐ መታጠብ አለበት፡፡ ንስሐውም እንደ ሮማዊው መቶ አለቃ ፍፁም ራስን ዝቅ በማድረግ፣ በትህትና የሚፈጸም መሆን አለበት፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቅፍርናፎም በገባ ጊዜ አንድ መቶ አለቃ ቀርቦ ልጁን እንዲያድንለት ለመነው፤ ጌታችን ወደ መቶ አለቃው ቤት ሄዶ ልጁን እንደሚፈውስለት በነገረው ሰዓት ትሁት፣ ተነሣሂ ልቦና ነበረው መቶ አለቃ “አቤቱ! አንተ ከቤቴ ጣራ በታች ልትገባ አይገባኝም፡፡” (ማቴ. 8፡8) በማለቱ ጌታችን አመስግኖታል፡፡ እኛም የከበረ የክርስቶስ አካል ቤት በተባለ ሰውነታችን በቅዱስ ቁርባን አማካኝነት እንደሚገባ ሲነገረን እንደ ጸሐፍትና ፈሪሳውያን በትዕቢት ሳይሆን እንደ መቶ አለቃው በትህትና፣ ኃጢአታችንን በመናዘዝ “አቤቱ! አንተ በእኔ በኃጢአት በከረሰ ሰውነት ልታድር አይገባህም፣ እንደ ቸርነትን አንጻኝ፣ ቀድሰኝ” ልንል ይገባል፡፡ ለዚህም እንዲረዳን በመንፈስ ቅዱስ የተቃኙ አባቶቻችን ወደ ቅዱስ ቁርባን ለመቅረብ የሚጸለዩ ልቦናን ከምድራዊ ሀሳብ ከፍ የሚያደርጉ፣ ትምህርተ ሃይማኖትን የጠነቀቁ ጸሎቶችን አዘጋጅተውልናል፡፡
    ስለሆነም የሚቆርቡ ምዕመናን ከመቁረባቸው በፊት የሚጸለየውን ጸሎት ይጸልዩ ዘንድ ይገባል፡፡ ቅዱስ ቁርባንን ካህናት፣ ሕጻናት፣ ደናግል፣ ሕዝባዊያንና ምዕመናን ቤተክርስቲያን የሠራችላቸውን ቅደም ተከተል ጠብቀው ይቆርባሉ፡፡ ሥጋውን ካህኑ በእጁ ሲያቀብል ደሙን ንፍቅ ካህኑ በዕርፈ መስቀል ለካህናት እንዲሁም ዲያቆኑ ለምዕመናን በዕርፈ መስቀል ያቀብላል፡፡ ንፍቅ ካህን ሥጋውን አያቀብልም፡፡ ንፍቅ ዲያቆንም ደሙን ለማቀበል አይችልም፡፡ የአቆራረብ ቅደም ተከተላቸውም ቅድሚያ በመቅደስ ውስጥ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት፣ ቆሞሳት፣ ቀሳውስት፣ ዲያቆናት ሲቆርቡ በቅድስት ደግሞ የሚጠቡ ሕጻናት፣ ወንድ ልጆች፣ ሴቶች ልጆች፣ አዋቂ ወንዶችና አዋቂ ሴቶች ይቆርባሉ፡፡ በመጨረሻም ማየ መቁርር (የቅዳሴ ጠበል) ቅዱስ ቁርባንን ለተቀበሉ ወዲያውኑ ይሰጣቸዋል፡፡ ከዚያም ከቁርባን በኋላ የሚጸለየውን ጸሎት ይጸልያሉ፡፡

    ቅዱስ ቁርባን ከተቀበልን በኋላ ምን ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል?

    ቅድስት ቤተክርስቲያን የሰርግ ቤት ትባላለች፡፡ በሰርግ ቤት የሙሽራና የሙሽሪት ተዋሕዶ (አንድነት) እንደሚፈጸም በቅድስት ቤተክርስቲያንም የሙሽራው የክርስቶስና የሙሽራይቱ የቤተክርስቲያን ተዋሕዶ (አንድነት) ይነገርባታል፣ ይፈጸምባታል፡፡ (ኤፌ. 5፡21-33) የሰው ልጅ በልማዱ ከሌሎች ሰዎች ጋር በሚሆንበት ጊዜ ራሱን ባማረ ልብስ ያስውባል (ታስውባለች)፡፡ በተለይም ደግሞ ወደ ሰርግ ቤት የተጠራ እንደሆነ ልዩና ያማረ ሰርግ ልብስ መልበስ ይገባል፡፡ በወንጌል ትርጓሜ የሰርግ ቤት የተባለች ቅድስት ቤተክርስቲያን ነች፡፡ የሰርጉ ማዕድም የክርስቶስ ቅዱስ ሥጋ፣ ክቡር ደም ነው፡፡ ጌታችን በወንጌል እንዳስተማረ ሙሽራው ባለበት የሰርግ ቤት የሰርግ ልብስ ሳይለብሱ በአልባሌ አለባበስ መገኘት ያስወቅሳል፣ ያስቀጣል፡፡ (ማቴ. 22፡11-13)
    ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “እንግዲህ የክርስቶስን አካል ወስዳችሁ የአመንዝራ አካል ታደርጉታላችሁን? አይገባም፡፡” (1ኛ ቆሮ. 6፡15) እንዳለ የክርስቲያን ሰውነት በክርስቶስ ሥጋና ደም የከበረ ነውና ሁልጊዜም በንጽሕና፣ ከኃጢአት በመራቅ መጠበቅ አለበት፡፡ በተለይም በቅዱስ ቁርባን ከክርስቶስ ጋር በምንዋሐድባቸው ዕለታት ከሌሎች ጊዜያት በበለጠ ጥንቃቄ ራሳችንን ከኃጢአት ልንጠብቅ ይገባል፡፡ ይህም ባሏን የምትጠብቅ ንጽሕት ሙሽራን ይመስላል፡፡ አንዲት ሴት ምንጊዜም ራሷን በንጽሕና መጠበቅ እንዳለባት ቢታወቅም ባሏን ለተዋሕዶ በምትጠብቅበት ዕለት ግን በተለየ ሁኔታ ራሷን ትጠብቃለች፡፡ እኛም ራሳችንን የክርስቶስ ሙሽራ አድርገን በንስሐ ተጸጽተን ሥጋውን ከበላን ደሙን ከጠጣን በኋላ ልናደርጋቸው የሚገቡንን ጥንቃቄዎች የክርስቶስ አካል ቅድስት ቤተክርስቲያን ደንግጋልናለች፡፡
    በፍርድ በሙግት ጠብና ክርክር አይታጣምና ከዚያ ለመራቅ ከቆረቡ በኋላ በዚያው ዕለት ወደ ፍርድ ቤት መሄድና መሟገት ክልክል ነው፡፡ ከመንፈሳዊ ሀሳብ ይልቅ ለስጋዊ ደስታ የተመቸ ነውና በዚሁ ዕለት ለባለትዳሮች ሩካቤ፣ አብዝቶ መብላትና መጠጣት አየይገበባመም፡፡ ጥፍር መቁረጥ፣ ጸጉር መላጨት፣ በውኃ መታጠብና ከልብስ መራቆት ክልክል ነው፡፡ ግብፃውያን ክርስቲያኖች በቆረቡበት ዕለት በባዶ እግር አይሄዱም፡፡ እንቅፋት እንዳያገኛቸውና እግራቸው እንዳይደማ ነው፡፡ እንዲሁም ከቁርባን በኋላ የጸሎት መጻሕፍትን ያነባሉ፡፡ ተረፈ ዕለቱንም ከሰዎች ጋር ባለመገናኘት፣ በሰላምና ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ ያሳልፋሉ፡፡
    ከቆረቡ በኋላ በተለይም ከጥንቃቄ ጉድለት የተነሳ እንቅፋት (መሰናክል) እክል ቢያጋጥመን ለምሳሌ. ነስር፣ እንቅፋት፣ ትውከት፣ ወደ አፍ የሚገባ ትንኝ፣ ዝንብ… ቢያጋጥመን፤ ንስሃ ልንገባና ያጋጠሙንን እክሎች በሙሉ ለካህን (ለንስሃ አባታችን) ልንናገር ይገባል፡፡የተሰጠንን ንስሃም ሳንፈጽም ዳግም መቁረብ አይፈቀድም (አይገባም)፡፡ ሩቅ መንገድ መሔድ፣ መስገድ፣ አይገባም፡፡ ይህም ምስጢሩ በሥጋ ወደሙ ድካም የለበትምና፡፡ አንድም በመንግስተ ሰማይ ከገቡ በኋላ ድካም የለምና አንድም ድኀነት በሥጋና በደሙ ሳይሆን በትሩፋት ነው እንዳያሰኝ ነው፡፡

    ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስለምስጢረ ቁርባን የምታምነው እምነት ከሌሎች የሚለየው እንዴት ነው?

    ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስለምስጢረ ቁርባን የምታምነው እምነት አማናዊ ለውጥ (Definitive change) ሲሆን ይህም ‹ፍጹም በሆነ አምላካዊ ምስጢር ኅብስቱ ተለውጦ አማናዊ የክርስቶስ ሥጋ፣ ጽዋውም ተለውጦ አማናዊ የክርስቶስ ደም ይሆናል›› የሚል ነው፡፡ ይህም የሰው አእምሮ ተመራምሮ የማይደርስበት አምላካዊ ምስጢር ነው፡፡ ከተለወጠም በኋላ ነፍስ የተለየው መለኮት የተዋሐደው ሥጋና ደም ይሆናል፡፡ ይህንንም ተቀብለን ከክርስቶስ ጋር አንድ አካል እንሆናለን፡፡ የካቶሊክ እምነት ደግሞ ‹‹ተፈጥሮአዊ በሆነ ለውጥ (Transubstantiation) የኅብስቱና የወይኑ ተፈጥሮ ወደ ሥጋና ደም ይቀየራል›› የሚል ነው፡፡ በእነርሱ እምነት ለውጡ በውጫዊ ገጽታውና በውስጣዊ ይዘቱ ላይ አይታይም፡፡ ተቀይሮም ሙሉ ክርስቶስን (ሥጋ፣ ደም፣ ነፍስና መለኮት ያለው) ይሆናል ብለው ያምናሉ፡፡ በሌላ በኩል ሉተራንስ ብሎ ራሱን የሚጠራው ዋናው የፕሮቴስታንት ክንፍ ስለ ቁርባን የሚያራምደው እምነት ‹‹ምስጢራዊ ኅብረት (Sacramental Union)›› ይባላል፡፡ ይህም የክርስቶስ ሥጋና ደም ከኅብስቱና ከወይኑ ጋር አብሮ በኅብረት ይገኛል የሚል ሲሆን የሚቀበሉትም ሥጋውና ደሙን እንዲሁም ኅብስቱንና ወይኑን አብረው ይቀበላሉ ብለው ያምናሉ፡፡
    በአንጻሩ ተሃድሶአውያኑ ደግሞ ‹‹በመንፈስ መገኘት (Spiritual Presence)›› የሚል አስተምህሮ አላቸው፡፡ ይህም በቁርባኑ ላይ ክርስቶስ በአካል አይገኝበትም፤ በመንፈስ እንጂ የሚል ነው፡፡ ስለዚህም በኅብስቱና በወይኑም የሚካሄድ የተፈጥሮ/ይዘት ለውጥ የለም ብለው የሚያምኑ ሲሆን ከቁርባኑ ጋር ያለው መንፈስም የሚቀበሉትን ክርስቲያኖችን ከክርስቶስ ጋር ያገናኛቸዋል ይላሉ፡፡ ሌላው በቁርባን ላይ ያለው እምነት የተለያዩ አዳዲስ የእምነት ድርጅቶች የሚያራምዱት ‹‹መታሰቢያነት (Memorialism)›› የሚለው ነው፡፡ ይህም ኅብስቱና ወይኑ የክርስቶስ ሥጋና ደም መታሰቢያ ምልክቶች ብቻ ናቸው የሚል ትምህርት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ኅብስቱንና ወይኑን የሚቀበል የክርስቶስን መታሰቢያ ያደርጋል የሚሉ ሲሆን ክርስቶስ በክርስቲያኖቹ ኅሊና እንጂ በኅብስቱና በወይኑ አይገኝም ብለውም ያስተምራሉ፡፡ በእነርሱ እምነት የቁርባን ሥርዓቱ ምልክትና መታሰቢያ ብቻ ነው፡፡ በመጨረሻም ቁርባን የሚባለው የእግዚአብሔር ቃል እንጂ የሚበላና የሚጠጣ አይደለም (Real Absence) የሚል አስተሳሰብ ያላቸው ወገኖችም አሉ፡፡ እኛ ግን አምላካችን ክርስቶስ ያስተማረውንና የሠራልንን የምስጢረ ቁርባን ሥርዓት መሠረት አድርገን በአማናዊው የክርስቶስ ሥጋና ደም (ነፍስ የተለየው መለኮት የተዋሐደው) እናምናለን፡፡

    ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ለምን ለየብቻ ይዘጋጃል?

    ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ለየብቻ እንጂ ተቀላቅሎ አይዘጋጅም፡፡ ይህም የጌታችንን የምስጢረ ቁርባን ትምህርትና የሠራውን ሥርዓት መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ጌታችን “ሥጋዬን የሚበላ” ሲል ቅዱስ ሥጋውን እንድንበላ፣ ከዚያም “ደሜን የሚጠጣ” ሲል ደሙን እንድንጠጣ መናገሩ ነው፡፡ እንዲሁም “ሥጋዬ እውነተኛ መብል ደሜም እውነተኛ መጠጥ ነው” ብሎ ለይቶ የተናገረው ተለያይቶ እንዲዘጋጅ ነው፡፡ ሥርዓተ ቁርባንን በሠራባት በጸሎተ ሐሙስም በመጀመሪያ ኅብስቱን አንስቶ ባረከና ቆርሶ ሰጣቸው፤ ከዚም ጽዋውን አንስቶ አመስግኖ ስጣቸው፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ለየብቻ ተዘጋጅቶ በመጀመሪያ ቅዱስ ሥጋውን ቀጥሎ ክቡር ደሙን እንቀበላለን፡፡

    ሳይገባው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን የሚቀበል ቅጣቱ ምንድን ነው?

    ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው ሳይገባው (ሳይዘጋጅ) የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም የሚቀበል ዕዳ አለበት፡፡ ካህኑ እንዳወጀው ተጠያቂው ራሱ በድፍረት የተቀበለው ሰው ነው፡፡ የካህኑ አዋጅ የሚጠቅመው “ባለማወቅ ነው የተቀበልኩት” እንዳንልም ነው፡፡ እዚያው ካህኑ ተናግሮታልና፡፡ ይህንን የካህኑን ቃል ተዳፍሮ የሚቀበል ግን ዲያቆኑ እንደተናገረው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ያሳዝናል፡፡ “ስለበረከት ፈንታ መርገምን ስለኃጢአት ሥርየት ፈንታ ገሃነመ እሳትን ይቀበላል” የድፍረት ኃጢአት ከሁሉ የከፋ ነውና፡፡

    ጌታችን ሥጋውና ክቡር ደሙን “ለመታሰቢያ አድርጉት” ያለው ምን ማለት ነው?

    የድኅነትን ነገር መቀለጃ የሚያደርጉ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ምስጢር ከእምነት በተለየ ደካማ ፍጥረታዊ አዕምሮ ለመረዳት የሚሞክሩ የወንጌል ጠላቶች በወንጌል ያልተጻፈውን አንብበው፣ የተጻፈውን አዛብተው እውነተኛ የክርስቶስ ሥጋና ደም “መታሰቢያ ብቻ” ነው በማለት የማይገባቸውን ይናገራሉ፡፡ ይሁንና ጌታችን ኅብስቱን ባርኮ ሲሰጣቸው ‹‹ይህ ሥጋዬ›› ነው በማለት ነው እንጂ መታሰቢያ ነው በማለት አይደለም፡፡ ጽዋውንም አንስቶ አመስግኖ ሲሰጣቸው ‹‹ይህ ደሜ ነው›› አላቸው እንጂ መታሰቢያ ነው አላለም፡፡ ሐዋርያት የእምነታችው ጽናት የሚደነቀው ኅብስቱን እያዩት ‹‹ሥጋዬ ነው›› ወይኑንም እያዩት ‹‹ደሜ ነው›› ቢላቸው የሚሳነው ነገር እንደሌለና በግብር አምላካዊ ‹‹አማናዊ ሥጋና ደም›› እንደሚሆን ያለጥርጥር መቀበላቸው ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ለመታሰቢያዬ አድርጉት›› ያለው ዘወትር ምዕመናን ለምስጋና ለመስዋዕት (ሊቆርቡ) በተሰበሰቡ ጊዜ ሞቱን ግርፋቱን ትንሣኤውንና ዕርገቱን እንዲያስታውሱ ለማሳሰብ ነው፡፡
    ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ይህንን የሐዋርያትን ትምህርት ሳታፋልስ፣ ሳትጨምርና ሳትቀንስ በቅዳሴ ጊዜ ‹‹ንዜኑ ሞተከ እግዚኦ ወትንሣኤከ ቅድስት/አቤቱ ሞትህንና ቅድስት ትንሣኤህን እንናገራለን›› እያለች ማንሳቷ ለዚህ ጽኑ ምስክር ነው፡፡ ጌታችን ለመታሰቢያዬ አድርጉት ሲል ‹‹ቅዱስ ቁርባንን በተቀበላችሁ ጊዜ የተደረገላችሁን ሰማያዊ ፍቅር አስቡ›› ማለቱ ነው እንጂ ‹‹ቁርባን መታሰቢያ ነው›› ማለቱ አይደለም፡፡ መታሰቢያዬ አድርጉት ማለትና መታሰቢያ ነው ማለት የተለያየ ነው፡፡ ደካማ አዕምሮ ባላቸው ሰዎች አነባበብ ከተወሰደ “መታሰቢያ” የሚል ስያሜ ያላቸው ሰዎች “እውነተኛ አይደሉም” ይባል ይሆን? መታሰቢያ ብቻ ቢሆን ኖሮ ሳይገባው የተቀበለ ሁሉ ዕዳ አለበት አይባልም ነበር፡፡ ብዙዎች ታመዋል፣ አንቀላፍተዋል የተባለው መታሰቢያ የሆነውን ሳይገባቸው ስለተቀበሉ ይሆንን? ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ለመታሰቢያዬ አድርጉት›› የሚለውን ሲያብራራ ‹‹ይህንን እንጀራ በበላችሁ ጊዜ ሁሉ፣ ይህንንም ጽዋ በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ጌታ እስሚኪመጣ ድረስ ሞቱን ትናገራላችሁና›› በማለት ገልጾታል፡፡ 1ኛ ቆሮ 11፡25-26

    ካህናት አባቶች ለምን ሥጋውና ክቡር ደሙን ይሸፍኑታል?

    በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሥርዓት የጌታችን ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ይሸፈናል፡፡ ይህም ቅዱስ ዮሐንስ የጌታችንን ስዕል ለጢባርዮስ ቄሳር ሲሥል በመጀመሪያ ጌታችንን ልክ እንደተሰቀለ አድርጎ ራቁቱን ነበር የሳለው፡፡ ዮሐንስ የሳለው የጌታችን ሥዕልም አፍ አውጥቶ “በመጀመሪያ አይሁድ በኢየሩሳሌም ራቁቴን ሰቀሉኝ፣ አሁን ደግሞ አንተ ድጋሚ በሮም ራቁቴን ትሰቅለኝን?” ብሎ ተናገረው፡፡ ዮሐንስም እጅግ ደንግጦ ‹‹እንዴት አድርጌ ልሳልህ?›› ብሎ የሳለውን ሥዕል ቢጠይቀው ሥዕሉም “ከለሜዳ አልብሰህ ሳለኝ” አለው፡፡ ዮሐንስም እንዳለው ከለሜዳ አልብሶ ሳለው፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ በከለሜዳ ምሳሌ ይሸፈናል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ጌታችን በተሰቀለ ጊዜ የፈጣሪያቸውን እርቃን ላለማሳየት ፀሐይ ጨልማ ጨረቃም ደም ለብሳ ነበር፡፡ ይህንንም አብነት በማድረግ ካህናት ሥጋና ደሙን ይሸፍኑታል፡፡

    ስለምን ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን ደጋግመን እንድንቀበል አስፈለገ? ስንት ጊዜስ እንቁረብ?

    ምስጢረ ቁርባን የሚደገም ምስጢር ስለሆነ አንድ ክርስቲያን በሕይወቱ ይህን ያህል ጊዜ ይቁረብ ባይባልም በየጊዜው ግን ንስሐ እየገባ ከመምህረ ንስሐው ጋርም እየተማከረ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ሊቀበል ይገባዋል፡፡ ሁሉም ክርስቲያን ሲጠመቅ ቅዱስ ቁርባንን ቢቀበልም ከተጠመቀ በኋላ ለሚሠራው ኃጢአት ማስተስረያ ንስሐ ገብቶ ቅዱስ ቁርባንን መቀበል ያስፈልገዋል፡፡ ባለትዳሮችም በተክሊል ሥርዓታቸው ወቅት ቅዱስ ቁርባንን ቢቀበሉም በትዳር ሕይወታቸውም በየወቅቱ ከመምህረ ንስሐቸው ጋር እየተመካከሩ ንስሐ እየገቡ ቅዱስ ቁርባንን ይቀበላሉ፡፡ ሰው በንስሐ ታጥቦ ቅዱስ ቁርባንን ከተቀበለም በኋላ መልሶ ኃጢአትን ይሠራልና ምስጢረ ቁርባንን ደጋግሞ ይፈጽማል፡፡ ይህንን ያህል ጊዜ ባይባልም በዓመት ውስጥ ክርስቲያኖች ቢያንስ በታላላቅ በዓላት (ልደት፣ ጥምቀት፣ ትንሣኤ…..) መቁረብ ይኖርባቸዋል፡፡

    ሐዋርያት የቆረቡት ከምግብ በኋላ ምሽት ላይ ሆኖ ሳለ ለምን እኛ ቅዱስ ቁርባን ለመቀበል እንጾማለን?

    የዚህ ጥያቄ መንፈስ “ከሐዋርያት ጋር ፉክክር” ያለ ያስመስላል፡፡ በመሠረቱ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንደሚያስተምሩት ‹‹የጸሎተ ሐሙስ ዕለት አስቀድመው የፋሲካውን በግ ከበሉ በኋላ በግብር አምላካዊ አስቀድመው የበሉትን አጥፍቶ ለበረከት ካመጡለት ከኅብስቱና ከወይኑ ከፍሎ “ይህ ሥጋዬ ነው፣ ይህ ደሜ ነው” ብሎ ለውጦ ትኩስ ሥጋ ትኩስ ደም አድረጎ አቁርቧቸዋል›› በማለት አመስጥረው ነፍስ የተለየው መለኮት የተዋሐደው አድርጎ እንደሰጠን አስተምረውናል፡፡ በወንጌል እንደተጻፈ ቅዱስ ዮሴፍ ዘአርማትያስ ጌታችን እንዲቀበርበት የመረጠው መቃብር “በውስጡ ሰው ያልተቀበረበት አዲስ መቃብር ነበር፡፡” (ዮሐ. 19፡41) እኛ ደግሞ ስንቆርብ የምንቀበለው ዮሴፍና ኒቆዲሞስ እንደገነዙት ነፍስ የተለየው መለኮት የተዋሐደውን የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም እንደሆነ ቅድስት ቤተክርስቲያን ታስተምራለች፡፡ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ በአዲስ መቃብር ጌታችንን እንደቀበሩት ከቅዱስ ቁርባን የሚቀበሉ ምዕመናንንም አፋቸውን ምሬት እስኪሰማቸው (ሆዳቸው ባዶ እስኪሆን) ለ18 ሰዓታት በመፆም እንዲቆርቡ ቅዱሳን አባቶቻችን ሥርዓትን ደንግገውልናል፡፡

    መስዋዕት የሚባለው ራሱን ቤዛ አድርጎ የተሰቀለው መድኃኔዓለም ወይስ ቅዱስ ቁርባን?

    የዚህ ዓይነት ጥያቄ የሚመነጨው በኢየሱስ ክርስቶስና በቅዱስ ቁርባን መካከል ያለውን ግንኙነት ካለመረዳት ነው፡፡ ሥጋ ወደሙን ከኢየሱስ ክርስቶስ ለይቶ ማየት ደግሞ ምስጢረ ተዋሕዶን ያለመረዳት ነው፡፡ በመሠረቱ በሥጋ ወደሙና በጌታችን መካከል ስላለው ግንኙነት ያስተማረን ራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እንዲህ ሲል ‹‹እንካችሁ ብሉ ይህ ሥጋዬ ነው አለ፡፡ ጽዋውንም አንስቶ አመስግኖም ሰጣቸው እንዲህም አለ፡- ሁላችሁ ከእርሱ ጠጡ ስለብዙዎች ለኃጢአት ይቅርታ የሚፈሰ የአዲስ ኪዳን ደሜ ነው፡፡›› ማቴ 26፡ 26 ታዲያ ራሱ ጌታችን የነገረንን ትተን የሰዎችን ፍልስፍናና ተረት እንቀበልን? እኛስ የምንቀበለው ቅዱስ ቁርባን ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ ሆኖ የተገለጠ የመድኃኔዓለም የኢየሱስ ክርስቶስ አማናዊ መሥዋዕት መሆኑን በፍጹም ሃይማኖት እንቀበላን፡፡ ይህ ግን የምንመገበው የተሰዋው አንድ ጊዜ ነው፡፡ አሁንም የምንሳተፈው ከዚያው አንድ ጊዜ በርሱ በራሱ ከቀረበው ሆኖ አምነው በመቅረብ ግን ዘወትር ለሚመገቡትም የዘላለም ሕይወትን የሚያስገኝ ነው፡፡

    ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰው የነሳውን ሥጋ እንዴት ‹‹እንዴት የአምላክ ሥጋ የአምላክ ደም›› እንለዋለን? <

    ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ነፍስን የነሣው ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ረቂቅ የሆነው መለኮት የሰውን ሥጋና ነፍስ ፍጹም ስለተዋሐደና በተዋሕዶ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው ስለሆነ የሥጋ ገንዘብ የመለኮት ሆነ፤ የመለኮትም ገንዘብ ለሥጋ ሆነ፡፡ ቃል ሥጋ ሆኖአልና፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ነፍስ ስለተለየው እንደሚፈርስ፣ እንደሚበሰብስ የፍጡር አካል አይደለምና፡፡ ‹‹የአምላክ ሥጋ የአምላክ ደም›› እንለዋለን፡፡

    “ኢየሱስ ይፈርዳል፣ ሥጋውና ደሙ ያማልደናል” የሚሉትስ እንዴት ይታያል?

    በፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮ የደነዘዙ ሰዎች ክብር ይግባውና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከማዳን፣ ከቤዛነት ስራው ፍጻሜ በኋላም “አማላጅ” እንደሆነ አድርገው ይናገራሉ፣ ያስተምራሉ፡፡ ለዚህም እንዲረዳቸው የቅዱሳት መጻሕፍትን ንባብና ያበላሻሉ፣ ትርጓሜውን ይለውጣሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ከሚታወቁባቸው አስተምሮዎቻቸው መካከል ቀደምት አበው ያቆዩዋቸውን አዋልድ መጻሕፍት በውኃ ቀጠነ መተቸት አንዱ ነው፡፡ ምንም እንኳ አዋልድ መጻሕፍትን የሚጠሉና የሚንቁ ቢሆኑም “ሰይጣን ላመሉ መጽሐፍ ቅዱስን ይጠቅሳልና” እነርሱም ለክህደታቸው የሚመች ከመሰላቸው የአዋልድ መጻሕፍትንም አጣምመው ለመጠቀም ይሞክራሉ፡፡ በዚህ አግባብ ከሚጠቅሷቸው ደገኛ የቤተክርስቲያን መጻሕፍት አንዱ ቅዳሴ ሐዋርያት ነው፡፡ “ኢየሱስ ያማልዳል” የሚለውን አዘምነው “ኢየሱስ በዙፋኑ ተቀምጦ እንደሚፈርድ እናውቃለን፤ያማልዳል የምንለው በሥጋውና በደሙ(በቅዱስ ቍርባን) ነው” ይላሉ።
    ለዚህም የሚጠቅሱት ንባቡን እንጂ ትርጓሜውን ሳይመለከቱ “ስለ እኔ በቀራንዮ የፈሰሰ ንጹሕ የሚሆን የመሢሕም ደም እነሆ ስለ እኔ ይጮኻል፤ ይህ የሚናገር ደም የእኔን የባሪያህን ኃጢአት የሚያስተሰርይ ይሁን” የሚለውን ነው። ይህ ገጸ ንባብ የሚገኘው በቅዳሴ ሐዋርያት ቍጥር 106 ላይ ነው። የቅዳሴው አንድምታ ትርጓሜ ግን “የሚጮህ የሚካሰስ ዋጋ እንደሚያሰጥ ዋጋዬን (የዘለዓለም ሕይወትን) ይሰጠኛል ማለት ነው” ብሎ ምሥጢራዊ መልእክቱን ነግሮናል። ምክንያቱም ጌታችን “ሥጋዬን የሚበላ፥ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው”ብሎናልና ነው (ዮሐ 6፡53)። በቅዳሴው “የሚጮህ ደም የሚናገር ደም”ተብሎ የተነገረው ሥጋውና ደሙ (ቅዱስ ቍርባን) ነፍስ የተለየው መለኮት ግን የተዋሐደው ሕያውና ዘለዓለማዊ መሆኑን ለመመስከር ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ “በሥጋ ሞተ በመንፈስ (በመለኮት) ግን ሕያው ሆነ (ነፍስ ሥጋን እንደተለየችው ሕያው መለኮት አልተለየውም)” ያለው ይኼንን ነው (1ኛ ጴጥ 3፡18)። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም፡-የክርስቶስ ሥጋውና ደሙ መለኮት የተዋሐደው መሆኑን ሲመሰክር “የእግዚአብሔር ደም” ብሎአል (የሐዋ፡20፡28)።
    ለመሆኑ “ኢየሱስ ይፈርዳል፥ ሥጋውና ደሙ ያማልዳል፤” ማለት ምን ማለት ነው? በእርሱና በሥጋ ወደሙ መካከል ልዩነት አለ እንዴ? እርሱ ሌላ፥ሥጋውና ደሙ ደግሞ ሌላ ነው? እንዲህ ዓይነቱ አካሄድ አንዱን ክርስቶስ ለሁለት ከፍለው (በተዋህዶ ከሁለት አካል አንድ አካል፥ ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ የሆነውን አንዱን ክርስቶስ ሁለት ባሕርይ አድርገው) በሥጋው ወደ ሠርግ ቤት ተጠራ፤ በመለኮቱ ደግሞ በተአምር ውኃውን ወደ ወይን ጠጅነት ለወጠ” እንደሚሉ ውጉዛን ካቶሊካውያን መሆን ነው። ምክንያቱም ወደ ሠርግ ቤት የተጠራውም ተአምር ያደረገውም ከተዋህዶ በኋላ መለየት የሌለበት አንዱ ክርስቶስ ነው። እኛም የምንቆርበው በተዋህዶተ መለኮት የከበረውን፥ የአንዱን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋና ደም ነው፤ እርሱም የዘለዓለምን ሕይወት የሚሰጥ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡-“የምንቆርበው ቅዱስ ቍርባንበዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ ከተቆረሰው የክርስቶስ ሥጋና ደም ጋር አንድ ነው” ያለው ለዚህ ነው። 1ኛ ቆሮ 11፡29

    ሰዎችን ሥጋውንና ደሙን እንዳይቀበሉ የሚያደርጓቸው ምክንያቶችና መፍትሔዎቻቸው ምንድን ናቸው? <

    ክርስቲያኖችን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እንዳይቀበሉ የሚያደርጓቸው ብዙ ምክንቶች ቢጠቀሱም ባለመቀበል የቀረውን ዋጋ ግን ሊመልሱት አይችሉም፡፡ ብዙውን ጊዜ የሚጠቀሱት ምክንያቶች ስለቅዱስ ቁርባን በሚገባ አለመረዳት፣ መቅሰፍት ያመጣብኛል ብሎ መፍራት፣ ከኃጢአት አልተለየሁም (አልበቃሁም) ማለት፣ ከቆረብኩ በኋላ መልሼ ኃጢአት እሠራለሁ ማለት፣ እንዲሁም ስሸመግል እቀበላለሁ ማለት እና የመሳሰሉት ናቸው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ኢየሱስም በሰማ ጊዜ አላቸው። የታመሙ እንጂ ጤነኞች ባለ መድኃኒትን አይሹትም። ነገር ግን ሂዱ እወቁትም ይህ ምንድር ነው ኃጥአንን ወደ ንስሓ ልጠራ መጣሁ እንጂ ጻድቃንን ለመጥራት አልመጣሁምና” (ማቴ.9:12-13) እንደተባለው ይህ መድኃኒት ለታመሙት ነውና ከምክንያተኝነት ወጥተን ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን ልንቀበል ይገባል፡፡
    ክርስቲያን ስለ ምስጢረ ቁርባን የሚማረውና የሚያውቀው በዕውቀት ላይ ተመሥርቶ ራሱን እንዲያዘጋጅና ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ተቀብሎ የዘላለም ሕይወትን እንዲወርስ ነው፡፡ “ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው” እንደተባለ ሥጋውን የሚበላ ደሙንም የሚጠጣ በክርስቶስ ይኖራል፡፡ ሥጋውን ያልበላ ደሙንም ያልጠጣ ግን ለዘለዓለም የዘላለም ሕይወትን አያይም፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል እንጂ ላለመቀበል ምክንያትን ማቅረብ የዘላለም ሕይወትን አያሰጥምና ሁሉም ክርስቲያን ንስሐ እየገባ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ሊቀበል ይገባዋል፡፡ ስለ ኃጢአታችን ራሱን ቤዛ ያደረገ፣ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ ያዳነን፣ በዕለተ አርብ በቀራንዮ አደባባይ ራሱን ከአዳም ጀምሮ እስከ ዓለም ፍጻሜ ላሉ ሰዎች ሁሉ ቤዛ፣ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበ፣ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ በቤተክርስቲያን መሥዋእት ህልው ሆኖ የሚኖር፣ በደላችንን የሚያጠፋ፣ መሥዋዕታችንን የሚቀበል ልዩ የሐዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋውን በልተን ደሙን ጠጥተን በዘላለም ሕይወት ለመኖር ርስታችን መንግስተ ሰማያትን እንወርስ ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ አሜን፡፡

    ምንጭ፡ አስተምህሮ ዘተዋሕዶ